Wednesday, August 29, 2012

የመለስ ቀልዶች (sep, 30 2010)

ወያኔ ጉባኤውን አዳማ ላይ አካሄደ።

እናም ጉባኤው በአትሌት ሃይሌ ገብረስላሴ ንግግር ተቋጨ። መለስ ዜናዊም በሃይሌ ንግግር ሲስቅ በቴሌቪዥን ተመለከትነው። መለስ ዜናዊ፣ “በአምስት አመታት አጠናቅቀዋለሁ” ያለውን ትንግርታዊ፣ አስማታዊና ሰማያዊ የልማት እቅድ ዶክተር ሃይሌ ከመለስ ብሶ፣ “በሁለት አመታት እንጨርሰዋለን” ሲል ቃል ገባ። አያይዞም አትሌት ሃይሌ፣ “ስለ ሰከንድ ማሰብ አለብን” ሲል ተናገረ።
ሃይሌ ሃብቱንም ሆነ ክብሩን ያገኘው ባቋራጭ ሳይሆን፣ ላቡን ጠብ! አድርጎ በመሆኑ አከብረዋለሁ። የሃይሌ ክብር የግሉ ሳይሆን የሃገሪቱ ጭምር በመሆኑ ደግሞ ለሃይሌ ያለኝ አክብሮት ድርብ ነው።


ሻለቃ ሃይሌ ወደ ወያኔ ጉባኤ ሄዶ ያደረገውን የተሳከረ ዲስኩር ግን አልወደድኩለትም። በዚህ ድርጊቱ ሃይሌን የመኮነን ፍላጎት የለኝም። ጉባኤው ላይ ያድረገውን ንግግር አምኖበት ነው ብዬም አላስብም። ሃይሌ ከወያኔ ሰዎች የሚደርስበትን ጫና በቅርብ ከሚያውቁት አንዱ ስሆን፣ ገንዘብ በጥሬው እንዲያመጣ ጭምር እንደሚያስገድዱት መረጃዎች አሉ።
ሃይሌ ገንዘብ ለባለስልጣናቱ የሚሰጠው በምትኩ ሌላ ጥቅም ለማግኘት ሳይሆን፣ የችግር ወሬ እያወሩ ገንዘብ እንዲሰጣቸው ስለሚጫኑት ነው። በዚህ በወያኔ ዘመን ባለገንዘብ ከሆንክ የግዴታ አጠገብህ ለሚገኝ ባለስልጣን ግብር መክፈል አለብህ። ይህ በስውር የፀደቀ የስርአቱ ህግ ነው።

ሆኖም ሃይሌ አዳማ በተካሄደው የኢህአዴግ ጉባኤ ላይ ተገኝቶ ያንን ግራ የተጋባ ንግግር ያደርግ ዘንድ ያስገደደው አልነበረም።
“ጉባኤያችሁን በማጠናቀቃችሁ፣ እንኳን ደስ ያላችሁ” ብሎ ብቻ አመስግኖ በዘዴ ሹልክ ብሎ ማምለጥ ይችል ነበር።
ባለቅኔ መንግስቱ ለማ “ለአረንጓዴው አብዮት አረንጓዴ እንቁላል ውለዱ” በሚል መርህ፣ የኢሰፓን ምስረታ በግጥም እንዲያሞግሱ ሲጠየቁ እንዴት ሸውደው እንዳለፉ የምንረሳው አይደለም። ጳውሎስ ኞኞም፣ “ሰርቶአደር ጋዜጣን ትወደዋለህ ወይ?” ተብሎ ሲጠየቅ ምን እንደመለሰ አንረሳውም። ምን ነበር ያለው?

“ማርያምን ትወዳታለህ ወይ?” ተብሎ የሚጠየቅ ሰው ምን ብሎ መለሰ?
“ከግንድ የሚያላጋ ልጅ እያላት እንዴት ነው የማልወዳት?”

በርግጥ እየሱስ ክርስቶስ የፍቅር አምላክ ነው። ጳውሎስ ኞኞ አባባሉን ለማጣፈጥ ያለው ይሆናል።
ሃይሌ ግን በየዋህነት ለመለስ ቀልድ ተመቸ። ጉባኤው ላይ ቀርቦ፣ በደቂቃ ልዩነት አንድ ሚሊዮን ዶላር ስለማግኘትና ስለማጣት መፈላሰፍ ባላስፈለገው ነበር። የአትሌቲክስን የማሸነፍና የመሸነፍ ልምዱን ቀመር እንደ ወረደ አምጥቶ የሃገሪቱ የኢኮኖሚ አጀንዳ ላይ አለበሰው።

በሃይሌ ንግግር መለስ ከአንጀቱ ሲስቅ አይተነዋል። መለስ የሳቀው በሃይሌ ንግግር ተደስቶ ሳይሆን፣ በሃይሌ የዋህነት ተገርሞ መሆን አለበት። ምክንያቱም እዚያ ጉባኤ ላይ የሚበተነው የልማት ተስፋና አበባ በመጪው አምስት አመታት እንደማይፈፀም መለስ ዜናዊ አሳምሮ ያውቅ ነበር።

ይህን ካሰብኩ በሁዋላ ጥቂት ተከዝኩ። እናም አንድ የካህሊል ጊብራን ወግ ትዝ አለችኝ። መጽሃፉ አጠገቤ ስለሌለ በራሴው መንገድ ላውጋችሁ፣

በጥንት ዘመን አንድ አማኝ ቄስና ኢአማኒ ፈላስፋ የአንድ ከተማ ነዋሪዎችን ሰብስበው በእግዚአብሄር ጉዳይ ላይ ክርክር ያካሂዱ ነበር።

አማኙ ቄስ “እግዚአብሄር ፈጣሪ አምላካችን ነው” ሲል መፅሃፍ ቅዱስን እየጠቀሰ ረጅም ሰአት ሰበከ።

ኢአማኒው ፈላስፋ በበኩሉ “እግዚአብሄር የሚባል ነገር የለም። የሰው ፈጠራ ነው” ብሎ ህዝቡን ለማሳመን ሲፈላሰፍ ዋለ።

ሙግቱ እንዳበቃ ተሟጋቾችም፣ ህዝቡም ወደየቤቱ ተበተነ።

አማኙ ቄስ ታዲያ ቤቱ እንደገባ መፅሃፍ ቅዱሱን አቃጠለና ከዚያች እለት ጀምሮ “እግዚአብሄር የለም” ሲል ደመደመ።
ኢአማኒው ፈላስፋ በበኩሉ ቤቱ እንደደረሰ መሬት ላይ ተንበርክኮ እንዲህ ሲል ፀለየ፣

“አምላኬ ሆይ! በዛሬው እለት አንተ ፈጣሪዬ እንደሆንክ አመንኩ! እስከዛሬ ስለካድኩህ ይቅር በለኝ!!”