Wednesday, August 29, 2012

መለስ ዜናዊ ከሞት እንዴት እንዳመለጠ (March 5 2012)

ትረካውን ጥቂት አሰማምሬው ይሆናል እንጂ ይህ የምገልፅላችሁ ታሪክ በትክክል የተፈፀመ ነው። ታሪኩን ካጫወተኝ ሰው ጋር ስናወራ፣
“ልፃፈው?” ስል ጠየቅሁት።
ሳቀ! በጣም ሳቀ! እና ፈቀደልኝ።
“ፃፈው! ድክመታችንን ያሳያል …” አለ።


* * *

ባጭር ጊዜ ውስጥ የታቀደ ነበር። በረቀቀ ጥበብም ሁኔታዎች ተስተካክለዋል። የቀረ ነገር ቢኖር በእቅዱ መሰረት መለስ ዜናዊ ላይ አደጋውን የሚጥል ደፋር ሰው ማግኘት ብቻ ነበር። የማጥቃት እቅዱን ለመፈፀም የታሰበው በጦር መሳሪያ አልነበረም። በቡጢ ነበር። አንድ ሃይለኛ ቡጢ! በቃ!

ቦታው ብራስልስ ነው። የአውሮፓ ህብረት ስብሰባ ላይ መለስ እንደሚገኝ ተረጋግጦአል። መረጃው አስተማማኝ ነበር። ለማስተማመኑ ማረጋገጫው መለስ ዜናዊ የሚቀመጥባት መቀመጫ ጭምር መታወቋ ነበር። የሆነው ሆኖ መለስ ላይ አደጋውን የሚጥል ሰው ለማግኘት ጥቂት ሰአታት ወስዶአል። ደግነቱ ከእቅዱ አዘጋጆች አንዱ፣

“እኔ እፈፅመዋለሁ! ደህና ቡጢ አቀምሰዋለሁ፣ ወይም አሰንብተዋለሁ!” አለ።

የዚህን ሰው እውነተኛ ስም መግለፅ አልፈልግም። ለትረካው እንዲያመቸኝ ግን ሙላቱ ብዬዋለሁ። ባጭሩ ደግሞ “ሙሌ!” እንለዋለን። እና ይህን ተግባር ለመፈፀም ሙሌ ሃላፊነቱን ወሰደ።

እነሆ! ዝግጅቱ ተጠናቆአል። ሙሌ ወደ ስብሰባ አዳራሹ ጋዜጠኛ ሆኖ ይገባ ዘንድ የመግቢያ ወረቀት አጊኝቶአል። ካሜራ አንገቱ ላይ አንጠለጠለ። ግንባሩን ቋጠረ። ሙሌ ረጅም ሲሆን፣ እጁ ረጅምና እንደ ወይራ ጥምዝዝ ያለ ነበር። ከአዘጋጆቹ አንዱ መከረው፣

“ሙሉ ሃይልህን አታሳርፍበት። ዋናው መልእክታችንን ማስተላለፍ ነው” አለው።

ሙሌ በዚህ አልተስማማም።

“ከሰነዝርኩማ እጠረምሰዋለሁ። ነካክቶ መተው አላውቅበትም”

ርግጥ ነው፣ መለስን አንድ ጥሩ ቡጢ ማቅመስ አለምን የሚያዳርስ ዜና ይሆናል። በተለይ ደግሞ መለስ ዜናዊ በየእስርቤቱ የሚያስደበድባቸው የዴሞክራሲ ታጋዮች፣ የሚደርስባቸውን ህመም እሱም እንዲቀምሰው ከተደረገ ሊሰማው ይችላል። ካልቀመሰው እንዴት ሊሰማው ይችላል?

የስብሰባው ሰአት እየተቃረበ በሄደ መጠን የሙላቱ ቁጣ እየጨመረ ሄደ። መለስ ይቀመጣል ተብሎ የተገመተበትን ቦታ በካርታ ጭምር ሲያጠና ቡጢውን እንደጨበጠ ነበር። እንባው ኮለል ብሎ ሳይወርድም አልቀረም። እንዲህ ያሉ እንባዎች ከቁጭት ኩሬ የሚፈልቁ ናቸው።

የመጨረሻዋ ሰአት እንደተቃረበች ሙሌ፣

“ይህን ታሪካዊ ድርጊት የምፈፅመው እንደ ልደቱ አያሌው ባንዴራ ለብሼ መሆን አለበት” የሚል አሳብ አቀረበ። ይህ ግን ተቀባይነት ሳያገኝ ቀረ። ስሜታዊ መሆን እንደማይገባ ተነገረው። ተራ ጋዜጠኛ ሆኖ፣ በስልት ወደ መለስ ዜናዊ መጠጋት እንዳለበትም ተመከረ። ለማንኛውም በሚል ሙሌ በተደጋጋሚና በልዩ ልዩ ቅርፅ ፎቶ እንደዲነሳ ተደረገ….

የስብሰባው ሰአት ደረሰ። መሪዎች ገቡ። ጋዜጠኞችም ወደ ውስጥ ጎረፉ። ሙሌም እንደማንኛው ተራ ጋዜጠኛ ተቀላቅሎ ወደ ውስጥ ዘለቀ። ከስብሰባው ውጭ ያሉ ጋዜጠኞች ጊዜ ለመቆጠብ ለዜናው የሚሆኑ አንዳንድ ነጥቦችን በቁራጭ ወረቀት ላይ መያዝ ጀማመሩ፣

“… በመለስ ዜናዊ አገዛዝ የተበሳጨ አንድ ጋዜጠኛ የመለስ ዜናዊን ሁለት ከንፈሮች በቡጢ አነደደ!”

“… መለስ ዜናዊ የቡጢን ህመም ቀመሰ! በሆስፒታል እርዳታ እየተደረገለት ሲሆን ለህይወቱ ሳያሰጋው አይቀርም።”

“… የአይን ምስክሮች እንደገለፁት የሙላቱ ቀኝ እጅ የመለስ ከንፈሮች ላይ ባረፉባት ደቂቃ፣ ‘ጧ!’ የሚል የፍንዳታ ድምፅ ተሰምቷል።”

“… ከሃኪሞች የሾለከ ዜና እንደሚገልፀው የመለስ ከንፈር ከባድ የመተርተር አደጋ ደርሶበታል።”

“… የቤልጂየም ሃኪሞች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እርዳታ እያደረጉለት ነው”

“… የመለስ ጥርሶች አለመጎዳታቸው ታወቀ! ዝርዝሩን እንደደደረሰን እንገልፃለን…”

እደጅ የነበሩት የእቅዱ አዘጋጆች ውጤቱን ለመስማት በጥፍራቸው ቆመው እየጠበቁ ነበር። ትንፋሽ አጥሯቸው በመጠባበቅ ላይ ሳሉም ሙሌ ካሜራውን እንዳንጠለጠለ ተመልሶ ብቅ አለ፣

“ምነው?” ሲሉ ጠየቁት።
በረጅሙ ተነፈሰ።
“አጣኸው እንዴ?”
“ማየትማ አይቼዋለሁ።”
“እና ታዲያ ለምን አልመታኸውም?”

“ፎቶ የማነሳው በመምሰል ስጠጋው፣ እሱም ልመታው እንዳሰብኩ ገባው መሰለኝ ፍርሃቱን አይኖቹ ውስጥ አየሁ። ልመታው እችል ነበር። አጠገቡ ነበርኩ…”

በከበቡት ሰዎች ዙሪያ ጥልቅ ዝምታ ወደቀ። ቃል የሚተነፍስ ጠፋ። በዚህ ጊዜ ሙሌ እንዲህ ሲል ፀጥታውን ሰበረው፣

“ፎቶግራፍ ግን አንስቼዋለሁ። ካላመናችሁኝ ላሳያችሁ እችላለሁ!”