Wednesday, October 17, 2012

ከባህር የወጣች አሳ

ብርድ እንዳገረጣት - እንደ ወይራ ቅጠል፣
ድምፁ እንደሚሰማው፣ እንደ ክረምት ማእበል፣
በምልምል ግንድ ላይ፣ አንድ ዘለላ ቅጠል፣ ሆኜ የአሸንቋጦ፣
ነፋስ አወዛውዞ፣ ሊጥለኝ ነው ቆርጦ፣

(ግጥም - አሌክሳንድር ፑሽኪን)
- አያልህ ሙላቱ እንደተረጎመው -

ፖቶማክ ወንዝ ዳርቻ ከሚገኘው ሬስቶራንት በረንዳው ላይ ተቀምጣለች። ይህ ዋሽንግተን ዲሲ ነው። ወንዙን የተሻገረ ግን ቪሪጂኒያ ገባ ማለት ይሆናል። አይኖቿን አሻግራ ወንዙን በዝምታ ስታጤነው ቆየች። ከመኖሪያዋ ርቃ ወደዚህ ሬስቶራንት የመጣችው ብቻዋን መሆን በመፈለጓ ነበር። ያዘዘችውን የሎሚ ጭማቂ ቀመስ አደረገችለት። እና እጇ ላይ ሲታሽ የከረመውን የቾምስኪ መፅሃፍ ለማውጣት ቦርሳዋን ስትከፍት አንድ መልከቀና ጎረምሳ በቀጥታ ወደሷ ሲመጣ ተመለከተች። በፈገግታ እንደተዋጠ እጁን ዘርግቶ ሰላምታ አቀረበላት። አላወቀችውም። ቢሆንም እሷም ፈገግ ብላ የተዘረጋላትን እጅ በትህትና ጨበጠች።
አበሻ ነሽ አይደለም?”
ልክ ነው
ብሩክ እባላለሁ
ብርቱካን
የጨበጠውን እጇን እንደያዘ፣
መቀመጥ እችላለሁ?” ሲል ጠየቃት።
ይቻላልአለች እያመነታች።
አስተናጋጁ ሲመጣ ብሩክ ቢራ አዘዘ። ከወፍራም ጥጥ የተሰራ ኒውዮርክ የሚል ፅሁፍ ያለበት ቤዥ ሹራብ ለብሶአል። በስፖርት የዳበረ ሰውነቱ፣ የለበሰውን ሹራብ አስጨንቆታል። በጄይል የታሹ የጠጉሩ ዘለላዎች እንደ ማረቆ ቃሪያ ጭራቸውን ጠቅልለው አናቱ ላይ ተጋድመዋል። የመካከለኛ ጣቱ ላይ ያጠለቀው የጉርጥ አይን የመሰለ ወፍራም ቀለበት ላይ ጥቁር ቀለም የተቀረፀው “B” ፊደል ፈርጥ ያብረቀርቃል
አይቼሽ አላውቅም። አዲስ ነሽ?” ሲል ጠየቃት።
ልክ ነው፣ አዲስ ነኝ። አንተስ?”
ሁለት አመት ሆኖኛል። በሜክሲኮ በኩል በእግር ነው የገባሁት። OLF ብዬ ነበር የፖለቲካ ጥገኛነት ጥያቄ ያቀረብኩት። አሽተው፣ አሽተው በመጨረሻ ሰጡኝ። አንቺስ?”
ብርቱካን ሳቀች። ከልቧ በመሳቋ ብሩክም የመዝናናት ስሜት አደረበት። በርግጥ ለምን እንደሳቀች አልገባውም። ለጠየቃት ጥያቄ መልስ አለመስጠቷንም ቢሆን ልብ አላለም። እና ወደ ሌላ ርእስ ከመዝለቁ በፊት እሷ ቀጠለች፣
የአዲስአበባ ልጅ ነህ?”
እንዴታ!? የዶሮ ማነቂያ ልጅ ነኝ። በርግጥ የተወለድኩት አሜሪካን ግቢ ነው። አንቺስ?
ፈረንሳይአለች።
! ፈረንሳይ ልጅ ነሻ!?” ብሩክ በጣም አዳነቀ፣ ከዚያም አልፎ አካበደ፣ “…10 ክፍል እያለሁ አንዲት የፈረንሳይ ልጅ ጠብሼ ነበር። ቁንጅናዋን ልነግርሽ አልችልም። እግሯ የሚመጠጥ ሸንኮራ። ዳሌዋ የሚገላበጥ ማእበል። ስትስቅ ጨረቃ። ከንፈሯ አይስክሬም። ብቻ ምን አለፋሽአንቺን ነበር የምትመስለውእየቀለድኩ እንዳይመስልሽ…
ብርቱካን መሳቋን በመቀጠሏ
ማርያምን!” አለና እጇን እንደመያዝ አደረጋት። ገፅታዋን አጤነና ግን መልሶ ለቀቃት። እና ንግግሩን ቀጠለ፣
“…ገና ስገባ ሳይሽ ማርቲ ናት ትዝ ያለችኝ። ማርታ ነበር ስሟ። አባቷ ገንዘብ የተረፈው ልጥጥ ነበር። የፈለግሁትን ጠይቄያት ታሽረኝ ነበር። ገና ስገባ ሳይሽ እኮ፣ማርቲን የመሰለች ልጅብዬ ተዋወቅሁሽ እንጂ፣ ስራ ነበረኝ።
ምንድነው የምትሰራው?” ስትል ጠየቀችው።
ታክሲ እሰራለሁ
አያያዘና ቀጠለ፣
ስምሽን ብርቱካን ስትይኝ ወዲያው ወደ ጭንቅላቴ የመጣውን ልንገርሽ? የኔ ስም ብሩክ ነው። ያንቺ ስም ብርቱካን። የሁለታችንም ስም፣ ‘B’ በሚለው መጀመሩ አጋጣሚው አይገርምም?”
ብርቱካን እንደገና በጣም ሳቀች። ብሩክም በሳቁ አጀባት። እና ወጉን ቀጠለ፣
አግብተሽ ነው የመጣሽው?”
ማለት?” አለች ግራ ተጋብታ።
“Citizen ፈርሞልሽ ነው አሜሪካ የመጣሽው?”
አይደለም…” አለች።
አግብተሽ ከሆነ የመጣሽው እንዳትወልጂለት ልመክርሽ ብዬ ነው። አዘናግተሽ ሽው ማለት ነው። አመቻችቶ፣ ‘ቻው!’ ማለት የተለመደ ነው። ሁሉም እንደሱ ነው የሚያደርገው። ካላገባሽ ግን ጣጣ የለውም። በይ የሆነ ነገር ጠጪ፣ እኔ ነኝ የምከፍለው…”
ብርቱካን ተጨማሪ ነገር ማዘዝ ባለመፈለጓ ብሩክ ለራሱ ሌላ ቢራ አዘዘ፣
የሚበላ ይምጣ?”
ምሳ ወስጃለሁ፣ አመሰግናለሁ።ካለች በሁዋላ፣ ግንባሯን ቋጠር አድርጋ ጠየቀችው፣
“2005 ላይ የት ነበርክ?”
ታሪኩን ባጭሩ አጫወታት።
ከኢትዮጵያ ከወጣ ዘጠኝ አመታት አልፎታል። ስደት የጀመረው በሱዳን በኩል ነበር። ሊቢያ ገባ። የመኖሪያ ወረቀት ስላልነበረው ተያዘና ሁለት አመታት ታሰረ። ጊዜውን ጨርሶ ሲፈታ ወደ ኬንያ አቀና በመቀጠል በኡጋንዳ በኩል ብሩንዲን በማቋረጥ በማላዊ ወንዝ ላይ በጀልባ ተጉዞ፣ ወደ ደቡብ አፍሪቃ ተሻገረ። ደቡብ አፍሪቃ ላይ ብዙ ስቃይ ገጥሞት ነበር። ህይወቱን አደጋ ላይ ጥሎ፣ ከቻይና ነጋዴዎች ጋር ጥሩ ቢዝነስ ሰራ። ደህና ገንዘብ ከያዘ በሁዋላ አስር ሺህ ዶላር ከፍሎ ሜክሲኮ ደረሰ። ከሜክሲኮ በእግር ጉዞ ድንበር ሰብሮ አሜሪካ ገባ። አሁን ዋሽንግተን ዲሲ ላይ ታክሲ ነጂ ሆኖአል። የዘጠኝ አመታት የጉዞ ታሪኩን እንዲህ ቀለል አድርጎ ነገራት። ታሪኩን ተርኮ ሲያበቃ የብርቱካንን ገፅታ መጨላለም እንኳ ሳያስተውል ወደ ሌላ ጥያቄ ተሸጋገረ፣
እስኪ ያንቺን ታሪክ ንገሪኝ?” ሲል ጠየቃት።
እንዳንተ የሚነገር ታሪክ እንኳ የለኝምአያያዘችና ቀጠለች፣ “….ትንሽ ሴት ልጅ አለችኝ። ሃሌ ትባላለች…”
ዋው!” አለ በአድናቆት፣ “….ፎቶዋ አለሽ?”
ከቦርሳዋ አወጣችና አሳየችው። ብሩክ በተመስጦ ካስተዋላት በሁዋላ፣
ቆንጆ ልጅ አለችሽአለ።
በመቀጠል የጠየቃት ጥያቄ ብርቱካን ይጠይቀኛል ብላ የጠበቀችውን አልነበረም።
አዲስአበባ ምን ትሰሪ ነበር?” ሲል ጀመረ፣
እንደማሰብ ካለች በሁዋላ፣ የመንግስት መስሪያ ቤት ውስጥ እሰራ ነበርስትል መለሰች።
ስራሽን ትተሽ ነው አሜሪካ የመጣሽው?”
አይደለም። ታስሬ ነበር…”
ታስረሽ ነበር?” በመደነቅ ጠየቃት።
የብሩክን የመገረም ምክንያት ለማወቅ ብርቱካን በጣም ጓጓች።
ብሩክ፣ እኔም አዲስአበባ ታስሬ ነበርካለ በሁዋላ ማብራራቱን ቀጠለ፣ “…በሚገርም ሁኔታ የኔና ያንቺ ታሪክ ተመሳሳይ ነው። እኔንም አስረው አሽተውኛል። ታደሰ የተባለ መርማሪ ወያኔ ነው የተጫወተብኝ። እንዴት ገልብጠው እንደገረፉኝ በሁዋላ ጀርባዬን አሳይሻለሁ።
ብሩክ እንደገና እጇን ለመያዝ እየሞከረ፣
“ዛሬ ከኔ ጋር ነሽ አይደለም? የራሴ ክፍል አለኝ። አንድ ደባል ብቻ ነው ያለኝ። ሌሊት ስለሚሰራ ብቻችንን ነው የምንሆነው…” እያለ ተለማመጣት።
ዳኛ ብርቱካን ሚደቅሳ እጇን በዝግታ ካስለቀቀችው በሁዋላ ጥያቄ ጠየቀችው፣
የት ነበር የታሰርከው?”
“6ኛ። አንቺስ?”
እኔ ቃሊቲ ነበርኩ። ለምን ነበር ያሰሩህ?”
የገንዘብ ጉዳይ ነው። ልጥጦች ጋር እሰራ ነበር። አዘናግቼ ደህና ፍሉስ ከነትኳቸው። ምን ያደርጋል፣ ከተያዝኩ በሁዋላ ጉቦ ከፍለው አስቀጠቀጡኝ። ቢሆንም ግን አላመንኩላቸውም። ምንም ማስረጃ አልነበራቸውም። በመጨረሻ ዳኛው በነፃ ለቀቀኝ።
በጣም ሲስቅ ቆየና እንዲህ ሲል ጠየቃት፣
አንቺስ ለምን ታሰርሽ?”
የፖለቲካ ጉዳይ ነው…”
ፖለቲካ!? ፖለቲከኛ ነሽ እንዴ? እኔኮ ጮካ መስለሽኝ ነበር።
እንደገና እጁን ሊይዝ ሞከረና መልሶ እራሱ ተወው። መጠየቁን ግን አልተወም፣
“አንቺ ግን ለምን ፖለቲካ ውስጥ ገባሽ?”
ስለ ቅንጅት ሰምተህ ነበር?ስትል ጠየቀችው።
ቅንጅት?” አለ ነቃ ብሎ፣ “…ስለ ቅንጅት እማ በደንብ አውቃለሁ። ቅንድቡን ወደላይ ዘርግቶ ቀጠለ፣ “…ልደቱ የሚባል ሰው ከእናንተ ጋር ነበረ አይደለም?” ሲል ጠየቃት።
እየሳቀች፣ልክ ነህአለችው።
በእርግጠኛነት እና በስሜት ማብራራቱን ቀጠለ፣
“… ወያኔዎቹ ለልደቱ አንዲት ንቅሳታም ትግሬ አጣብሰውት ከዳቸው ሲባል ሰምቻለሁ። እናንተ ግን ሸዋዬ ነገር ናችሁ። እንዴት ነቄ መሆን አቃታችሁ? ግን ልጠይቅሽ እስኪ አሁን ቅንጅት የት ነው ያለው?
ብርቱካን ከዚያ በላይ ከብሩክ ጋር መቆየት እንደማትችል አወቀች። በዚያችው ቅፅበት በድንገት ገፅታዋ የተለበለበ ግንድ መምሰሉንም ቢሆን ብሩክ አላስተዋለም በድንገት ለምን እንዲህ እንደተለወጠች መረዳትም አልቻለም። እና ብሩክ ግራ ተጋባ። ለመሄድ መፈለጓን በመግለፅ ስትሰናበተው ብሩክ፣ “ለመሄድ ከፈለገች ምን ይደረጋል?” በሚል እሱም ተሰናበታት። በርግጥ ለምናልባቱ በሚል የስልክ ቁጥሩ የተፃፈበት ካርዱን አስይዟታል። እንድትደውልለትም ተማፅኖአታል።
ብርቱካን ከሬስቶራንቱ ወጣች።
የዋሽንግተን ዲሲ ተስያት ጭጋጋማ ነበር። ጉሙ እስከ ወንዙ ወርዶአል። ብርቱካን በእግሯ አዘገመች። በድንገት አየሩ ተለወጠ። ለሆሳስ ያነበረው ንፋስ ማፉዋጨት ያዘ። ጭጋጉን ይበታትነው ጀመር። በርግጥ ረጅም ርቀት ማየት የሚቻል አልነበረም። ለቨርጂኒያ ጀርባዋን ሰጥታ መንገዷን ቀጠለች። ለአፍታ አሜሪካ ላይ፣ “ግማሽ ሚሊዮን ይደርሳል” ስለሚባለው አበሻ አሰበች። “ስንቶች ይሆኑ እንደ ብሩክ?” የሚል ጥያቄ አእምሮዋን አቋርጦ አለፈ። ሳታስበው፣ “አምላኬ” የሚል ቃል ካንደበቷ አፈትልኮ ወጣ። በለሆሳስ መፀለይ ፈልጋ ነበር። አልቻለችም። እንደ መብረቅ የተወረወረ ሽምጥ ነፋስ፣ ቃሉን ከከንፈሮቿ ላይ መንጭቆ ወሰደባት። ፍርሃት እና ብርድ ተቀላቅለው አንጀቷ ውስጥ የገቡ ያህል ውስጧ ቀዘቀዘ። እና ብርድ እንደበረታባት እርግብ ኩምትር አለች። ፖቶማክ ወንዝ ሲጓዝ ከጀርባ ሰማችው። እንደ ቢጫ ቅጠል አንስቶ ወንዙ ላይ ሊጨምራት እልህ ከተጋባው ነፋስ ጋር እየታገለች ወደፊት አዘገመች። የለም! የለም! ወደፊት አዘገመች ማለት እንኳ ይቸግራል። ነፋሱ ክፉኛ ወደሁዋላ እየገፋት ነበር…
(ተስፋዬ ገብረአብ፣ አጭር ልቦለድ ድርሰት - ነሃሴ፣ 2012