Friday, August 31, 2012

ጎሹም ሄደላችሁ… (April 17th, 2012 )

የኮሎኔል መንግስቱን መፅሃፍ ሳነብ ከገረሙኝ ነገሮች አንዱ የኮሎኔል ጎሹ ወልዴን ስም አለመጥቀሱ ነበር። ቢያንስ፣ “የታጠቅ ጦር ሰፈር አመሰራረት” በሚለው ምእራፍ ስር እንኳ ስሙን ሊያነሳው በተገባ።
በቂ ምክንያት ማቅረብ ባልችልም ስለ ኮሎኔል ጎሹ በጎ ስሜት አለኝ። ምናልባት የመንግስቱን ስርአት ተቃውሞ ስለኮበለለ እንደ ውለታ ቆጥሬለት ሊሆን ይችላል። ጊዜው አይረሳኝም። ጎሹ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ለቆ ሲኮበልል እኔ ደብረዘይት ነበርኩ።
በአየር ሃይልና በአየር ወለዶች የብረት ጫማ ቁጥጥር ስር የነበረችው ደብረዘይት በጎሹ ወልዴ የመኮብለል ወሬ ታምሳ እንደነበር አስታውሳለሁ። “የቡርቃ ዝምታ” ላይ እንደጠቀስኩት፣ ደብረዘይት ላይ የፖለቲካ ወሬ የሚከካው ከአየርሃይል ሆቴል ባንኮኒ ላይ ነበር። እዚያ የማይመጣ የለም። በተለይም ሁሉን አዋቂና አስፈፃሚ የሆኑት መስመራዊ መኮንኖች የሆቴሉ ቋሚ ደንበኞች ናቸው። ለሃሜቱና ለብልግናው ደብረዘይት ምቹ ናት። ዋዝጂፕ እያንኳኩ፣ ከጠመንጃና ከጥይት ፋብሪካ፣ ከአየር መቃወሚያና ከታንክ መገጣጠሚያው ወደ አየር ሃይል ሆቴል ይጎርፋሉ።
ኮሎኔል ጎሹ ወልዴ አገር ለቆ በኮበለለ ሰሞን ከሆቴሉ ባንኮኒ አካባቢ የሰማሁዋት ግጥም ዛሬም ድረስ ትታወሰኛለች፣
አትመንጥሩ፣ አትመንጥሩ – ደኑን ስንላችሁ፣
ነብሩም አንበሳውም – ጎሹም ሄደላችሁ…
ፖለቲካና ስነጥበብ ሲቀላቀሉ ያሳብዳል። እነዚህ ሁለት ስንኞች ለጎሹ ወልዴ ወገናዊነት እንዲሰማኝ ሳያደርጉኝ አልቀሩም። በዚያው ሰሞን ደግሞ ሌላ ወሬ ወደ አየር ሃይል ሆቴል ብቅ አለ። “ደቡብ ከሚገኘው እዝ 10 ሺህ ወታደሮች ከነትጥቃቸው ከድተው ኬንያ ገቡ” የሚል ነበር። ጎሹ ወልዴ ከአሜሪካ ወደ ናይሮቢ ተመልሶ፣ እነዚያን የከዱ የጦርሰራዊት አባላት እየመራ፣ በሞያሌ በኩል ወደ አዲስአበባ እየገሰገሰ ነው” ተባለ። በወቅቱ በጎረምሳነት መንፈስ፣ “እየገሰገሰ ነው!”፣ “በከበባ”፣ “በማጥለቅለቅ” የሚሉ ቃላት ይስቡኝ ነበር። ምናልባት፣ በ18ኛው ክፍለዘመን ገበሬ አደራጅቶ፣ ፒተርስቡርግን ከብቦ ንግስቲቷን ስላንቀጠቀጣት አመፀኛ ያነበብኩት በዚያው ሰሞን ስለነበር ሊሆንም ይችላል።
ምን ያደርጋል?
የጎሹ ወልዴ ሰራዊት “ከዛሬ ነገ አዋሳ ደረሰ” እያልን ብንጠብቅም ወሬው “የቆሪጥ ፉገራ” ሆኖ ቀረ። በግልባጩ እንዴት እንደሆነ እስከዛሬ ምስጢሩ ባልተነገረ ፍጥነት፣ እኔ ወያኔ ሆኜ፣ እኔ ባቀረብኩት ሃሳብ መሰረት፣ ወያኔ 25 አመታት መንገስ እንዲችል፣ ለቢሾፍቱ ቆሪጥ ነጭ ላም አርደንለት፣ ቆሪጥ “ለ25 አመት ንገሱ! አዲሳባ ግቡ!” ብሎ ስለፈቀደ እንደ ፓሎኒ ኳስ እየነጠርን አዲሳባ ገባን።
ከዚያም እንደገና የጎሹ ወልዴ ስም ተነሳ።
“መድህን የተባለ ፓርቲ መስርቶአል። ጎሹና ቢል ክሊንተን የትምህርት ቤት ጓደኛሞች ነበሩ። ወያኔ አለቀላት!” የሚል የወሬ ምላጭ ጆሮአችንን ሸረካከተው።
በዚህች አለም የህይወት መንገድ ላይ ህይወት ተገላቢጦሽ ስትሆን ብዙ ጊዜ አይቻታለሁ። ዛሬ ጎሹም ክሊንተንም የሉም። የነበረው ሁሉ እንዳልነበር ሟች ሆኖአል። ሟች መሆን ደባሪ ነው። ጎሹ “መድህን” የተባለ ድርጅቱን ለልደቱ በነፃ ሸጦለት ሲያበቃ፣ “ጴንጤ ሆኛለሁ ተውኝ!” ማለቱን ሰማሁ።
“ያ! ቆፍጣና ወታደር ምን ቢገጥመው ይሆን እንዲህ ባንዴ ፊቱ የጨለመ?” ብዬ ጠየቅሁ።
እምነት ላይ ጠበቅ ያሉ ጓደኞቼ፣
“…ተሳስተሃል! ጎሹ ዘላለማዊ የህይወት መንገድ አጊኝቷል። ለራስህ እወቅበት።” አሉኝ።
ፖለቲከኞቹ ጓደኞቼ ደግሞ፣
“…ጎሹን በነገር አሳብደው ከፖለቲካ የጨዋታ ሜዳ ያባረሩት ኢህአፓዎች ናቸው” ሲሉ ‘ምስጢር’ ነገሩኝ። ሁለቱም ምክንያቶች አልተዋጡልኝም። “ጎሹ ከራሱ እየሸሸ ነው” አልኩ።
ርግጥ ነው፣ ጎሹ ከተሰናበተ በሁዋላ ሌሎች ነብርና አንበሳዎች ተተክተው ነበር። ብዙዎች እየመጡ ሄደዋል። ያልቻሉ ተሰናብተዋል። የቻሉ ቀጥለዋል። ስድቡንም፣ ውግዘቱንም፣ ሃሜቱንም ችለው የነፃነትን ብርሃን በሩቅ እያዩ የሚጓዙ አሉ። ህዝብ ምንጊዜም ተስፋ አይቆርጥም። የደከሙትን እየሸኘ አዳዲሶችን ይወልዳል። ቢሆንም ግን …ቢሆንም ግን…እንዲህ ባለው ጊዜ ቢያንስ አሳብን መሰንዘር በጎ በሆነ ነበር…