Wednesday, August 29, 2012

'የመለስ “ጠንካራ” ጐን! (April 27th, 2011 at )

ከጥቂት ቀናት በፊት ‘ብዙ ወንድምአገኝ’ ከካናዳ ስልክ ደውላ እንዲህ ስትል ጠየቀችኝ፣
“ምነው ጠፋህ ታዲያ?”
መልስ ከመስጠቴ በፊት በግሳፄ እንዲህ ቀጠለች፣
“በአመት አንድ መፅሃፍ መፃፍ በቂ ይመስልሃል? ከሃገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ጋር በተያያዘ ስለ ቀድሞ አለቆችህ አንድ ነገር ማለት አለብህ።”
ከአንጋፋዋ ጋዜጠኛ ጋር የስልክ ቆይታዬን ካበቃሁ በሁዋላ ኮምፕዩተሬ ላይ አዲስ ገፅ ገለጥሁና፣ “የመለስ ደካማ ጎን!” የሚል ርእስ አሰፈርኩ።
የለም! የለም!
ስለ መለስ ደካማ ጎኖች ብዙ ተብሎአል። አል – ማርያምን ጨምሮ ሌሎች በርካታ የፖለቲካ ጉዳይ ተንታኞች የመለስንም ሆነ የቡድኑን ደካማ ጎኖች በበቂ ተንትነዋል። ኦባንግ ሜቶ፣ ገላሳ ድልቦ፣ ብርሃኑ ነጋ፣ አረጋዊ በርሄ፣ ጌታቸው ጂጂ፣ ፈቃደ ሸዋቀና፣ መስፍን ወልደማርያም፣ ግደይ ዘርአፅዮን፣ ሌንጮ ለታ፣ አንዳርጋቸው ፅጌ፣ አሰፋ ጫቦ፣ እስክንድር ነጋ፣ ወንድሙ መኮንን እና ሌሎችም በመፅሃፍና በመጣጥፍ መለስን ገለባብጠው አሳይተውናል። ገና ወደፊትም ብዙ እናነባለን። በዚህ መጣጥፍ መለስ ላለፉት 20 አመታት ስልጣን ላይ ለመቆየት የተጠቀመበትን የአመራር ጥበብ ምስጢር እና ጠንካራ ጎኑን በጨረፍታ ለመነካካት እሻለሁ። እና ርእሱን ለወጥኩት።
* * *
የአንድን ግለሰብ ወይም ቡድን፣ “ጠንካራ ጐን” ወይም “ደካማ ጐን” ስንገልፅ እንደየአመለካከታችን ሊለያይ ስለሚችል ላንግባባ እንችላለን።
ለአብነት በኢህአዴግ ውስጥ አማራና ኦሮሞን የወከሉት አባዱላና አዲሱ በሕወሓት አለቆቻቸው ዘንድ እንዴት እንደሚታዩ ማየት ይቻላል።
በኢህአዴግ የፖሊት ቢሮ ግምገማ ላይ፣ የአባዱላ ገመዳ ጠንካራ ጐን፣ “ታማኝነቱ!” ደካማ ጎኑ ደግሞ፣ “የአቅም እጥረቱ!” እየተባለ ላለፉት 15 አመታት ሙሉ ሲነገር ነበር። በተገላቢጦሽ ሰፊው የኦህዴድ አባል አባዱላ ታማኝነቱን ቅድሚያ ለመለስ በማድረጉ ሲነቅፉት ቆይተዋል። በዚህ መካከል ‘አባዱላ ራሱን እንዴት ማየት እንዳለበት ተቸግሮአል’ የሚል ወግ እየሰማን ነው። በመለስ ቡድን የግምገማ መለኪያ፣ ‘ለህዝብ ታማኝ መሆን’ ደካማ ጎን ተብሎ እንደሚያስፈርጅ አባዱላ ከራሱ ልምድ ለመገንዘብ እድል አጊኝቷል። ከህዝብ በፊት ለድርጅትህ ታማኝ መሆን የኢህአዴግ ቀዳሚ መርህ ነው።
አዲሱ ለገሰ ከልቡም ሆነ ከጨጓራው ሕወሓትን ያፈቅራል። ለዚህ አፍቅሮቱ የተሰጠው ስያሜ፣ “ከትምክህተኛነት የፀዳ” የሚል ሲሆን፣ ይህም “የአዲሱ ለገሰ ጠንካራ ጎን” እየተባለ ለዘመናት እምቢልታ ሲነፋለት ኖሮአል። ጠንካራ የተባለው የአዲሱ ባህርይ እውነተኛ ስም፣ “አድርባይነት” እንደሚባል ግን መለስ በልቡ ያውቃል። ጮሌው መለስ መልስ በኪሱ ብቻ ሳይሆን፣ ሙያውን በልቡ የመያዝ ጠንካራ ጎንም አለው።
ለመነሻ ያህል የመለስን ሰብእና በጨረፍታ እንገምግም ከተባለ መለስ፣ “ለእውነት ሟች” ከሚባሉ ሰዎች ተርታ ሊመደብ አይችልም። በአንፃሩ አስመሳይ ነው። ኢህአዴግንም በተመሳሳይ በአስመሳዮች ሞልቶታል። ገና ደርግ ሳይወድቅ በማሌሊት ዘመን የተጣባውን ልማድ ዛሬም ድረስ ይዞት ዘልቆአል። ማሌሊት የተባለው ፓርቲ ድንገት ከምድረገፅ ከመሰወሩ በፊት እንዲሁ በአፈ ጮማዎች ተሞልቶ፣ “ክብሩ ይስፋ መድሃኔአለም! ማሌሊት ተወለደልን!” እያሉ የሚያመሰግኑ የዋህ ቄሶች ሳይቀሩ በአባልነት ተመልምለው ነበር።
መለስ ዜናዊ፣ “መጥፎም ይሁን ጥሩ አላማ ያለውን ሰው አከብራለሁ” ብሎ ሲናገር ሰምቼዋለሁ። ይሄ እውነት አይደለም። በድርጅቱ ውስጥ የሰበሰባቸው ካድሬዎች አብዛኞቹ አድርባዮች ናቸው። የአሁኖቹማ ብሶባቸው መለስ ሲናገር በማያስቀው ጭምር ህብረ – ማስካካቱን ተላምደውታል። ቀደም ያሉት የድል ማግስት ዋነኛ አማካሪዎችም ቢሆኑ፣ የጭንቅላታቸውን መናገር የማይችሉ ታዛዦች ነበሩ። ተቀዳ አለሙ ሊጠቀስ የሚችል ማሳያ ነው።
ተቀዳ ለ19 አመታት የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር ሆኖ ሲሰራ የኢህአዴግ (ብአዴን) አባል ሆኖ አልተመዘገበም። በቅርቡ ስለዚሁ ጉዳይ ተጠይቆ ምላሽ ሲሰጥ በኢህአዴግ ስርአት ውስጥ የፓርቲው አባል ሳይኮንም ሃገርን ማገልገል እንደሚቻል ምስክርነት ሲሰጥ ሰምቼ በጣም ገርሞኛል። ይሄ ውሸት ነው። ኢህአዴግ አዲስአበባን ሲቆጣጠር የኢህአዴግ አባል ለመሆን ፈቃደኛ ከነበሩ ቀዳሚ ሰዎች ተቀዳ አንዱ ነበር። በወቅቱ ግን ‘የኢሰፓ አባላት ለኢህአዴግ አባልነት አይመለመሉም’ የሚል መመሪያ ወጥቶ ስለነበር፣ ተቀዳ በአባልነት ሳይመዘገብ እንዲቆይ ተወሰነ። መለስ እንደ ተቀዳ ያሉ ተጣጣፊ ሰብእና ያላቸውን ግለሰቦች በዙሪያው በማሰባሰቡ እሱ የሚያምንበትን ብቻ ማስፈፀም እንዲችል አድርጎታል። የተቀዳ መመፃደቅ ግን ከማስገመት ያለፈ ጥቅም አያስገኝም።
ሌላ ጊዜ ደግሞ መለስ “ጉረኛ ሰው አልወድም” ብሎ ሲናገር ሰማሁት። ይሄም ውሸት ነው። መለስ እራሱ የለየለት ቡፋ ነው። ቡፋነቱን የሚያሳዩ 101 አብነቶችን መደርደር ይቻላል።
ሩቅ ሳንሄድ በቅርቡ “የወር ደሞዜ 6400 ብር ነው” ብሎ ተናገረ። አያያዘናም እሱም እንደ ፋብሪካ ወዛደሮች የደሞዝ ጭማሪ እየጠበቀ መሆኑን አከለበት። የልብ ድካም ያለባቸው ሰዎች ይህን ቢሰሙ በብስጭት በዚያው ሊያመልጡ ይችላሉ። መለስ በ57 አመት እድሜው እንዲህ ያለ ጉራ አያምርበትም። ቢያንስ በአመት አንድ ሚሊዮን ብር የማይወራረድ ገንዘብ እንደሚበላ እናውቃለን። ይሄ ለ12 ወራት ተካፍሎ የወር ደሞዙ በአናቱ ሲታከልበት የመለስ የወር ደሞዝ 89 733 ብር ይመጣል። ይህ እንግዲህ በጥሬው የሚወስደው ነው። ለፕሮቶኮል መጠበቂያ ተብሎ የሚወጣው ሚሊዮናት ዶላር አይታሰብም። ለእሱና ለቤተሰቡ ህክምና፣ መዝናኛ እና የልጆች ትምህርት ቤት ክፍያ ሁሉ የሚፈፀመው ከደሞዙ ውጭ ከሃገሪቱ ጉሮሮ ነው። እንዲያው ሁሉም ነገር ይቅርና ባለፈው አመት ባለቤቱ አዜብ መስፍን ለመላ ቤተሰቧ የልብስ ወጪ 1.2 ሚሊዮን ዩሮ የከፈለችው ከየት አምጥታ ነው? ቤተመንግስት ውስጥ ዶላር የሚተፋ ዘንዶ ይኖራት ይሆን? ከዚህ ባሻገር የአዲሳባ ህዝብ ለአዜብ መስፍን፣ “የሙስና እናት” የሚል ቅፅል ስም እንደሰጣት መለስ ያውቃል ብዬ እገምታለሁ። “ህዝቡ ምናባቱ ያመጣል?” የሚል ንቀት አባይን ቀርቶ ተከዜን አያሻግርም። ስልጣን ሲበዛ ጭቆናና ዘረፋው እየበረታ እንደሚሄድ ከታሪክ የተማርነው እውነት ነው። ያም ሆኖ ዞሮ ዞሮ ግለሰቦች እንደ ጥላ አላፊ ናቸው። የሰው ልጅን አእምሮ እንዲደክም የሚያደርገው ፍርሃት ነውና፣ መሪዎችም ማለፋቸው ካልቀረ ከፍርሃት ነፃ የሆነ ትውልድ አፍርተው ቢያልፉ ይመረጣል።
* * *
ኢትዮጵያ በሶስት ሺህ አመታት ታሪኳ ከአድዋ መሪ ስታገኝ መለስ ዜናዊ ሁለተኛው መሆኑ ነው። የመጀመሪያው ከአድዋ የተገኘው መሪያችን ራስ ስሁል ሚካኤል ይባላል። ራስ ስሁል አፄ ኢዮአስን በሻሽ አንቆ ገድሎ የጎንደርን ስልጣን በእጁ ካስገባ በሁዋላ አቢሲንያን 40 አመታት እየረገጠ ገዝቶአል። እንደ አዲሱ ለገሰ እና አባዱላ ገመዳ ስሁል ሚካኤልም የጎንደርን አሻንጉሊት ባላባት ይሾምና ይሽር ነበር። ስሁል ሚካኤል በእጅጉ ጨካኝ ልብ ነበረው። ገድለ ታሪኩ እንደሚያወጋው ከሆነ፣ ስሁል በስተእርጅናው ዘመን አንድ ጊዜ ባላባቶችን ሰብስቦ እያናገረ ሳለ በመካከሉ እንቅልፍ ወሰደው። የጎንደር ባላባቶች እጅግ በጣም ይፈሩት ስለነበር ደፍሮ ከእንቅልፉ የሚቀሰቅሰው አልተገኘም። ስሁል ሚካኤል ጠረጴዛው ላይ እንቅልፉን ጠግቦ ሲነቃ ሚኒስትሮቹ በተቀመጡበት ሲቁለጨለጩ አገኛቸው። እናም እንዲህ ሲል ጠየቃቸው፣ “ክቡራን! እስካሁን ስልጣን ላይ ነን እንዴ?”
የመጀመሪያው የህወሃት መሪ ገሰሰው አየለ፣ የበረሃ ስሙን “ስሁል” ሲል የመረጠው የቀዳማዊው ስሁል አድናቂ ስለነበር ነው ይባላል። መለስ ዜናዊም ይኸው በቀዳማዊው ስሁል የአገዛዝ ስልት የዘመናችንን ሰው እየረገጠ መግዛት ከጀመረ ሃያ አመት ደፈነ። የስልጣን ዘመኑን ከቀዳማዊው ስሁል ወይም ከቆንጆይቱ ዮዲት ጉዲት ጋር ለማስተካከል ሃያ አመታት ብቻ ይቀሩታል። በርግጥ በመጪው ምርጫ እንደማይወዳደር ነግሮናል። በየአመቱ መታለል ስለሰለቸን ግን አናምነውም። መለስ ስልጣኑን ቢለቅ እንኳ፣ ጥርሰ ፍንጭቱን ሃይለማርያምን ከላይ ቁጭ አድርጎ፣ እሱ እንደ ፑቲን ከጀርባ ሆኖ፣ ሃይሌን እንደ ሜድቬዴቭ አስቀምጦ በእጅ አዙር መምራቱ አይቀርም። ከ2010 በሁዋላ ተመልሶ እንደማይመጣም ቢሆን ዋስትና የለንም።
በ16ኛው ክፍለዘመን ጥጋበኛው አፄ ልብነድንግል፣ “ጦርነት ናፈቀኝ፣ ጦር አውርድ!” እያለ መሬቱን በጅራፍ ሲገርፍ እግዚአብሄር ተቆጥቶ ይማም አህመድ ግራኝን እንደላከለት ታሪካዊ ተረት ሰምተን ነበር። የዚህ ዘመን ሰዎች ግን ነቄ! ስለሆንን እንዲህ ያሉ ተረቶችን ማመን ትተናል።
እግዚአብሄር እጅ፣ እግር እና አእምሮ ሰጥቶን ሲያበቃ፣ የምድርን ሃላፊነት ለኛው እንደተወልን ተመራምረን ደርሰንበታል። በመሆኑም የምንፈልገውን ማድረግ የኛ ፈንታ ነው። የማንፈልገውን ከተቀበልንም የኛ ድክመት ነው። በተቀረ መለስ ዜናዊን እግዚአብሄር አላመጣብንም። ስለዚህ እግዚአብሄር ከስልጣኑ አያነሳውም። በግድም ሆነ በውድ መለስን የማስወገዱ ተግባር እኛው ላይ የተጣለ ሃላፊነት ነው። እኛ ገፍተን ካልወረወርነው መለስ ዜናዊ እንደ ስሁል ሚካኤል ገና በእንቅልፍ ልቡ ሳይቀር ይገዛናል።
መለስም ቢሆን ስልጣኑን እግዚአብሄር እንዳልሰጠው አሳምሮ ያውቃል። ለስልጣን የበቃው በጭንቅላቱ ተጠቅሞ እንደሆነ ስለሚያምን፣ ስልጣኑን ሳያስነካ ለማስጠበቅ የቤት ስራውን ተግቶ ከመስራት ቦዝኖ አያውቅም። በመሰረቱ መለስ በእግዚአብሄር መኖር አያምንም። ስለዚህ ‘ሰው መግደል ሃጢአት ነው’ ብሎ ሊያስብ አይችልም። ‘የሰው ልጅ ከሞተ በሁዋላ ለዘልአለሙ በዚያው ሞቶ ይቀራል እንጂ፣ ከሞት ተነስቶ ለፍርድ አይቀርብም’ ብሎ የሚያምን ሰው ደግሞ ከህሊና ጥያቄ ነፃ መሆኑን መዘንጋት አይገባም።
እንደ ቡልቻ ደመቅሳ ያሉ ፈሪሃ እግዚአብሄር ያላቸው የፖለቲካ ሰዎች ከመለስ ጋር የፖለቲካ ቁማር መጫወቱን የተቸገሩት በዚህ የአመለካከት መራራቅ ምክንያት ነው። ከበደ ብዙነሽ በተመሳሳይ ጃንሆይ ላይ በሸፈቱ ጊዜ የሚያምኗትን ታቦት አሳይተው ነበር የማረኳቸው። ቡልቻ በባህርይ ትሁትና ይሉኝታ ያላቸው የተማሩ ጨዋ ሰው ናቸው። መለስ በአንፃሩ የገዛ ሚኒስትሮቹን፣ “ወዲ ሸርሙጣ!” እያለ የሚሳደብ ስድ፣ ባለጌ እና በትግርኛ ‘ወዲሹቕ’ የሚባል አይነት ኡላ ነው። ቡልቻ ሰላማዊ ሰው መግደል ይቅርና የሰው ሬሳ በአይናቸው አይተው የሚያውቁ አይደሉም። የኛ ዘመን ሰላማዊ ትግል ታሪካዊ ተረትና ታሪካዊ ፉገራ ሆኖ የዘለቀው፣ የገዢው ፓርቲና የሰላማዊ ትግል ታጋዮች መንፈስ እንደ ገፈርሳ እና እንደ ጨፌዶንሳ በመራራቁ ነው።
ከሰላማዊ ትግል ባሻገር የመለስን የአገዛዝ ስርአት የሚታገሉ ሃይሎች ጠንቅቀው መገንዘብ ያለባቸው እውነትም መለስ ከቲማቲምና ከእንቁላል ውርወራዎች ባሻገር፣ እሳት የሚተፉ አይኖችን ማየት እንደሚሻ ነው። እራሱ እንደተናገረውም ጀርባውን በእሳት አስገርፎ ያገኘውን ስልጣን፣ ከቲማቲም ለተሰራ ፈንጂ ደንግጦ የማስረከብ ዝንባሌ የለውም። ስልጣኑን ከማስረከቡ በፊት ጀርባውን በጋለ ሰንሰለት የሚገሸልጠውን ተቃዋሚ ማየት ይፈልጋል። ካልሆነ ግን በ2020 ላይ ከእንቅልፉ ባንኖ ሲያበቃ፣ ባለቤቱን ጠርቶ፣
“አዜብ! እስኪ ጅራፍ አምጪልኝና መሬቱን እንግረፈው?” ማለቱ አይቀሬ ይሆናል።
* * *
መለስ ዜናዊ ሃያ አመታት በስልጣን መቆየት የቻለበት አንድ የማይካድ ጠንካራ ጎን አለው። ይህም የተቃዋሚዎችን ደካማ ጎን በትክክል ማወቁ እና ያንን ደካማ ጎናቸውን በአግባቡ ሊጠቀምበት መቻሉ ነው። መለስ የተቃዋሚዎችን ደካማ ጎን በትክክል ማወቅ በመቻሉ የማጥቃት ርምጃዎቹን እያነጣጠረ በመተኮስ ቤተመንግስታዊ ግቢውን እስካሁን ሳያስደፍር መቆየት ችሎአል። እሱ የሚመራውን ቡድን ስስ ብልት ሳያስነካ ለመጠበቅም ከፍተኛ እድል አጊኝቷል።
መንግስቱ ሃይለማርያምን ከመለስ ጋር ስናነፃፅረው መንግስቱ ስሜታዊ ብቻ ነበር። “የባህር በር” እና “የሃገር አንድነት” የተባሉ ግዙፍ አጀንዳዎችን ይዞ እንኳ ስልጣኑን መጠበቅ ሳይቻለው ቀረ። መንግስቱን ለውድቀት ካበቁ በርካታ ምክንያቶች አንዱ፣ በጠላቶቹ ላይ ያሳደረው ንቀት ነበር።
የተቃዋሚዎቹን እና የራሱን ልክ በትክክል የማያውቅ መሪ በመሳሪያ ሃይልም ሆነ በአላማው ቀናነት ብቻ ቆሞ ሊቆይ ከቶውንም አይቻለውም። ቅን አላማ ብቻውን የትም አያደርስም። የነፃነት ትግል ውጤት እንዲያመጣ ከተፈለገ፣ ታክቲክና ስትራቴጂ ከመንደፍ ባሻገር ድርጊትና መስዋእትነትን ይጠይቃል።
መለስ የህዝብ ድጋፍ የለውም። ይህ የተረጋገጠ እውነት ነው። የህዝብ ድጋፍ ከሌለው እንዴት እስካሁን ስልጣን ላይ ሊቆይ ቻለ? “በጠመንጃ ሃይል” የሚሉ አሉ። አምባገነን መንግስታት የታጠቁት ጠመንጃ በሁለተኛ ደረጃ ሊታይ የሚችል መሆኑን ግን የአረቡ አለም አብዮት አሳይቶናል። መለስ ለ20 አመታት ስልጣን ላይ መቆየት የቻለው ለቢሾፍቱ ቆሪጥ ነጭ ላም ስላረደለትም አይደለም። ምላሹ አንድ ነው። የተቃዋሚዎችን ደካማ ጎን በትክክል ስለተጠቀመበት ብቻ ነው።
አንዳንድ ሰዎች፣
“አናሳው ቡድን እንዴት ሰፊውን ህዝብ ተቆጣጥሮ መዝለቅ ቻለ?” ሲሉ ደጋግመው ይጠይቃሉ።
ሌሎች ደግሞ፣
“እንጦጦ ላይ ቆመን ሽንታችንን ብንሸና ወያኔ ተጠራርጎ ይጠፋል” ብለው ፅፈው አንብቤያለሁ።
የዘመናችን ችግር “አንድ ነገር መናገር” ሳይሆን “አንድ ነገር ማድረግ አለመቻል” ሆኖአል። “እንጦጦ ላይ ቆመህ መሽናት” የሚባለው ምሳሌያዊ ንግግር እንደ አባባል ሲመዘን በእውነቱ ወርቅ ነው። ከአባባል ካላለፈ ግን አመድ ነው። አመድ ሆነው የቀሩ በርካታ አባባሎች ሞልተውናል። “በቃ!!” የሚለው አዲስ መሪ ቃል አመድ ሆኖ እንዳይቀር የመለስን የአመራር ጥበብ ማወቅ ግድ ይላል። “የመለስ የአመራር ጥበብ የተቃዋሚዎችን ደካማ ጎን ማወቅ መቻሉ ነው” የሚለውን አባባል መደጋገሜ አለምክንያት አይደለም። ይህ ነጥብ በቅጡ ሊብራራ ይገባዋል ብዬ ስለማምን ነው።
ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ሲባል፣ “ወያኔ አልቆለታል” ብሎ መፃፍና መቀስቀስ ተገቢ ሊሆን ይችላል። ፖለቲከኛው ራሱ፣ እራሱ የፃፈውን ፕሮፓጋንዳ አምኖ፣ “እውነትም ወያኔ አልቆለታል” ብሎ ካመነ ግን “ታጥቦ ተተኩሶ – ለጭቃ!” እንደማለት ይሆናል። የራስን ፕሮፓጋንዳዊ አባባል ከማመን ባሻገር፣ የወያኔ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ የመሆን ጉድለትም በስፋት ይታያል።
“መለስ ዜናዊ አዲስ ቤተመንግስት ማስገንባት ጀመረ” የሚለው ዜና በወርሃ መጋቢት ላይ ግንባር ቀደም ዜና ነበር።
ይህንን ዜና ቀድሞ በዝርዝር ያቀረበው የአማረ አረጋዊ ሪፖርተር ጋዜጣ ነበር። “አማረ እና ጌታቸው አሰፋ ይህን ዜና ተመካክረው ነው ያወጡት” ለማለት የሚያበቃ መረጃ የለኝም። ይሄ ዜና ድብቅ አላማ እንደነበረው ግን መረጃ አለኝ። ዜናው የተለቀቀበት ወቅት የአረብ ሃገራት መሪዎች ቤተመንግስታቸውን እየለቀቁ የሚሸሹበት ጊዜ ነበር። “ተረኛው ኮብላይ መለስ ዜናዊ ነው” የሚለው ትንበያም ተስፋፍቶአል። የመለስ የካቢኔ አባላትም ጭንቀት ውስጥ መግባታቸው ተሰምቶአል። በዚህ መካከል መለስ በአረብ ሃገራቱ አብዮት አለመደናገጡን የሚጠቁምለት አንድ ዜና መፈልሰፍ ነበረበት። “መለስ የኩብለላው ተረኛ ነው” የሚለው ወሬ፣ “መለስ አዲስ ባለመዋኛ ቤተመንግስት እየገነባ ነው” በሚለው እንዲተካ ሞከሩ። በነመለስ አስተሳሰብ ይሄ ዜና፣ ለተደናገጡት ደጋፊዎቹ ማረጋጊያ፣ የአመፅ ቅስቀሳ ለጀመሩ ተቃዋሚዎች ወሽመጥ መበጠሻ ሆኖ የታለመ ነበር። ይህ ዜና ለመለስ ጊዜያዊ ጭንቀት ማስተንፈሻ አገልግሎ ሊሆን ቢችልም፣ ሙከራቸው ግን አልሰመረም። ያም ሆኖ የተቃዋሚ ሜድያዎች ሳያውቁት ዜናውን በማሰራጨት የመለስ ተባባሪ ሆነዋል። ዜናዎች በዚህ መንገድ እንደሚፈበረኩ ሁሉ፣ እንደ አባይ ግድብ ያለ የመወያያ አጀንዳዎችም እየተዘጋጁ ይላኩልናል። እነዚህን ለይቶ ማወቅና ህዝቡን ማንቃት የፖለቲካ ሰዎች የስራ ድርሻ ነው።
“የመለስ ጠንካራ ጎን የተቃዋሚዎችን ደካማ ጎን በትክክል ማወቅ መቻሉ ነው” ብያለሁ። በአንፃሩ ተቃዋሚዎች የመለስን ቡድን ደካማ ጎን በትክክል ካወቁ በቀላሉ ሊያጠቁት ይቻላቸዋል። የመለስን ቡድን ደካማ ጎን በትክክል አለማወቅ ማለት፣ ለማጅራት ገትር በሽታ የወባ ኪኒን እንደ መስጠት ይቆጠራል። መለስ የሻእቢያን ስም ከአፉ የማይለየው፣ በዋነኛነት በጦር ሃይል ያጠቁኛል ብሎ ሰግቶ ሳይሆን፣ “ደካማ ጎኔን በትክክል ያውቁብኛል” ብሎ ስለሚያምን ነው። “ከአብሮ አደግህ – አብረህ አትሰደድ” ይላል ኦሮሞ ሲተርት።
ወደተነሳሁበት ዋና ነጥብ እየዘለቅሁ ነው።
ከአንድ አመት በፊት አንድ የኦነግ ሰው ቤቱ ራት ጋብዞኝ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮችን አንስተን ስንጨዋወት እንዲህ አለኝ፣
“…ደርግ የመሬት ላራሹን አዋጅ በማወጅ የኦሮሞን ህዝብ የመሬቱ ባለቤት አደረገው። ወያኔ ለኛ ብሎ ባይሆንም ለራሱ ሲል በቋንቋችን እንድንጠቀም ፈቀደ። መሬት እና ቋንቋ መሰረታዊ ጥያቄዎቻችን ነበሩ። ያልተመለሱ ቀሪ ጥያቄዎች ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ፣ አለያም የፍትህና የዴሞክራሲ ጥያቄ ናቸው። መሰረታዊ መብቶቻችንን ለማስጠበቅ የምናደርገውን ትግል ስለሚጠራጠሩት፣ ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ህብረት ለመፍጠር ተቸግረናል። ይህቺ ሃገር እኩል የምትደርሰን ከሆነ፣ ለደህንነቷም እኩል የሃላፊነት ስሜት ሊኖረን እንደሚችል መቀበል ይገባል። ዞሮ ዞሮ በቀጣዩ ጉዞ ከተግባባን ዴሞክራሲያዊ ስርአት አብሮ ያኖረናል።ካልተስማማን ግን ነፃነትን በግድ እናገኛለን”
መለስ ዜናዊ ላለፉት 20 አመታት አጤ ምኒልክ ቤተመንግስት መቆየት የቻለው እዚህ አካባቢ ያለውን ክፍተት እንደየሁኔታው ሊጠቀምበት በመቻሉ ነበር።
የሰሞኑ ግርግር መነሻውም ሆነ መቋጠሪያው ከዚህ አያልፍም። “ሻእቢያ አዲሳባን ባግዳድ ሊያደርጋት ነው” የሚለው ከበሮ ወዲያውኑ በመበሳቱ ከጥቅም ውጭ ሆኖአል። በመቀጠል “የአባይ ግድብ” ታላቅ ፈረሰኛ ዜና ሆኖ ብቅ አለ። መለስ ፓርላማ ላይ ቀርቦ፣ “ትንቢተ ዜናዊ” የተባለውን ምእራፍ በምርቃና ሲያምበለብለው በጥሞና አዳምጬዋለሁ። ነጥቦቹ ሲጨመቁ እንደሚከተለው ናቸው፣
• ግብፅ በራሷ የጦር ሃይል ታጠቃናለች ብለን አንሰጋም። በነጭ ለባሾች በኩል እንዳታጠቃን ግን እንሰጋለን።
• በአመለካከት ሊግባቡ የማይችሉ ሃይሎች ኦነግ፣ ኦብነግ፣ የደርግ ቅሪቶች እና የትምክህት ሃይሎች እኛን ለማጥቃት በሻእቢያ ካምፕ ውስጥ ተሰባስበዋል።
• አዲሱ እቅዳቸው አዲስአበባን ባግዳድ ማድረግ ሲሆን፣ ህዝብ በሚሰበሰብበት ቦታ ፈንጂ ለማፈንዳት እየሰሩ ነው። በዚህ ድርጊት ሻእቢያ ተጠቃሚ ሊሆን ይችላል። ኦነግ፣ ኦብነግ እና የትምክህት ሃይሎች ግን ምን ጥቅም እንደሚያገኙ አላውቅም።
• አዲሳባን ባግዳድ ለማድረግ የሽብሩን ተግባር ከአመፅ ተግባር ጋር አንድ ላይ ለማቀናጀት ዝግጅት እየተደረገ ነው።
የመለስ የፓርላማ ንግግር ዋና ነጥብ የመጨረሻዋ ብቻ ነበረች። ሌላው ሁሉ ማጀቢያ ነው። ህዝቡ ለአመፅ እንዳይነሳሳ፣ “ተጠንቀቅ! ፈንጂ ተደግሶልሃል።” ብሎ ሊያስፈራራ እየሞከረ ነበር። ይህች የመጨረሻዋ ነጥብም መለስ ምን አይነት ጭንቀትና ስጋት ውስጥ እንዳለ ልቡን ግልጥልጥ አድርጋ የምታሳይ ናት።
ኤርትራና ግብፅን እንተዋቸው።
‘ግብፃውያንና ኤርትራውያን አዲሳባ ላይ ፈንጂ ያፈነዳሉ’ ስላልተባለም አጀንዳችን ሊሆኑ አይችሉም። የግብፅና የኤርትራ ሚና ከጀርባ መሆኑን መለስ ስለተነተነ በግንባር ስላሉት እንነጋገር።
እንደ መለስ ትንተና ህዝብ በተሰበሰበበት ቦታ ‘ፈንጂ ያፈነዳሉ’ ተብለው የሚጠበቁት የኢትዮጵያውያን ተቃዋሚ ድርጅት አባላት እንማን ናቸው? በተለይም መለስ በዘዴ ጣልቃ ያስገባቸው “የትምክህት ሃይሎች” መሪዎች በግለሰብ ደረጃ ሲዘረዘሩ ማን ማን ይባላሉ? የጥቂቶችን ስም መጥራት ካስፈለገ፣ ወያኔ በጥቁር መዝገቡ ላይ ካሰፈራቸው መካከል፣ መስፍን ወልደማርያም፣ ነገደ ጎበዜ፣ ብርሃኑ ነጋ፣ ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ፣ አንዳርጋቸው ፅጌ፣ ነአምን ዘለቀ ሊጠቀሱ ይችላሉ። መሃመድ እስማኤል ኦማር እና የቤልጅየሙ መሃመድ ሃሰን፣ ዳውድ ኢብሳ እና ሃሰን ሁሴን፣ ቡልቱም ቢዮና በያን አሶባ የመሳሰሉት የኦጋዴን እና የኦሮሞ የፖለቲካ ሰዎችም አሸባሪ ተብለው ተመዝግበዋል። እነዚህ ናቸው መርካቶ ላይ ፈንጂ አፈንድተው ህዝብ ለመጨረስ በአንድ ካምፕ የተሰባሰቡት? ወይስ ሌሎች የማናውቃቸው ባለውቃቢና መናፍስት ይኖሩ ይሆን?
መለስ በፓርላማ ዲስኩሩ፣
‘እነዚህ ሰዎች ህዝቡ ላይ ፈንጂ በማፈንዳት ምን እንደሚጠቀሙ አላውቅም’ ማለቱ በጣም አስቂኝ ነበር። ከመነሻው የተጠቀሱት ሰዎች የሚደግፋቸውን ህዝብ በፈንጂ ለመጨርስ መቼ አቀዱና! ሃገሪቱን ለጅምላና ለችርቻሮ ገበያ ሲያቀርባት የነበረው ማን እንደሆነ ህዝቡ ያውቃል። የተሰመረበት የመለስ አባባል መለስ የቀድሞ ጮሌነቱን እንኳ አጥቶ ጭንቀት ውስጥ መግባቱን የሚጠቁም ነበር። የእውር ድንብሩንም የተቃዋሚዎችን የትብብር አስኳል ለማፍረስ በሙሉ አቅሙ እየተፍጨረጨረ ይገኛል።
በቅርቡ በሰሜን አሜሪካና በአውሮፓ የኦነግ፣ የኦብነግ እና የግንቦት ሰባት ደጋፊዎችና ሌሎችም የአገዛዙ ስርአት ተቃዋሚ ዜጎች፣ እንደ አንድ ሰውና እንደ አንድ ቡድን አፋኙን ስርአት በመቃወም ያሳዩት አስደናቂ ህብረት የመለስ ብቸኛ ጠንካራ ጎን ላይ የተተኮሰ የመድፍ ቁምቡላ ነበር ማለት ይቻላል። ተቃዋሚዎች ነባር ሆኖ የዘለቀ ዋነኛ ድክመታቸውን ማስወገድ ከቻሉ መለስ ብቸኛ የማጥቂያ ካርዱን ተነጥቆ ባዶ እጁን ይቀራል።
“ተቃዋሚ ሃይላትም ሆኑ ህዝቡ ‘በዘር የማትከፋፈል አንድ ኢትዮጵያ’ በሚለው ጃንጥላ ስር ቁጭ ብለው ሊነጋገሩ አይችሉም” ብሎ መለስ ዜናዊ በጥብቅ ያምናል።
ስለዚህ ተቃዋሚ ሃይላት የመሰባሰብ ሙከራ ሲያሳዩ ሙሉ ሃይሉን ያን ህብረት ከመበተን ላይ ያውላል። በዘር የመከፋፈያ አጀንዳዎች ቀላል እንደመሆናቸው ብዙውን ጊዜ ወያኔ አላማውን ለማሳካት ብዙ ችግር አይገጥመውም። ወያኔ ከቅንጅት ማእበል ይልቅ እጅግ አስደንግጦት የነበረው ኡትሬክት ላይ የተመሰረተው AFD እንደነበር ይታወሳል። ቅንጅት በበረታ ጊዜ ወያኔ ኦነግን እንደማስፈራሪያ ጭራቅ ስሙን እየጠራ ሊያስፈራራ መሞከሩ አይዘነጋም። ከማስፈራራትም በላይ በአዲሳባ ዙሪያ የሚኖሩ ኦሮሞ አርሶአደሮችን በኦነግ ስም በፈረሰኛነት አደራጅተው “አማራ ከመሬታችን ይውጣ!” በሚል መሪ ቃል አዲስአበባ ላይ ግድያና ዝርፊያ እንዲጀምሩ አዘጋጅቶአቸው ነበር። በወቅቱ ይህን ፕሮጀክት ለማስፈፀም ሲያስተባብር የነበረው አባዱላ ከህሊናው ታርቆ፣ የዚህን ያልተፈፀመ ፕሮጀክት ዝርዝር ሊያጋልጥ ከቻለ በኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ ከውለታ ሊቆጠርለት እንደሚችል አያጠራጥርም።
በወያኔ የመከላከያ ሰራዊት ውስጥ በተደረጉ በርካታ ግምገማዎች፣ አማራ እና ኦሮሞ ወታደሮች ላይ በተመሳሳይ ጊዜ የጠረጋ ዘመቻ የተፈፀመበት አንድም ጊዜ የለም። እንደየወቅቱ ትኩሳት እየታየ የፈረቃ ምንጠራ ሲካሄድባቸው ቆይቷል።
አማራዎች ሲመነጠሩ ለኦሮሞው፣
“…ነፍጠኛና ትምክህተኞችን እናፅዳ” የሚል ግብዣ ይቀርብለታል።
ኦሮሞችን ለመምታት ሲታቀድ ደግሞ፣
“የኦነግ አሸባሪዎችን እናስወግድ” በሚል መሪ ቃል አማራው ይቀሰቀሳል።
በዚህ መሃል የህወሃት ካድሬዎች መካከሉ ላይ እንደ ጆከር ሁሉም ዘንድ ይገባሉ። በዚህ መንገድ ከፋፍሎ ማስተዳደር የወያኔ የማይቀየር ስትራቴጂ መሆኑ ባለፉት ሃያ አመታት የታየና የተረጋገጠ ሆኖአል። ዜጎች ከክልል ወደ ክልል ተዘዋውረው እንዳይሰሩ ማድረግ ከተቀበሩት ፈንጂዎች ዋነኛው ነው።ተፈራ ዋልዋ፣ “ቆንጥር እየቧጠጣቸው ያገኙት ስልጣን ነውና ይገባቸዋል” እንዳለው በተመሳሳይ ጠበል የተጠመቁ ግለሰቦችን በዙሪያቸው ኮልኩለው፣ ሃገሪቱ ራሷን ችላ በእግራ እንዳትቆም የሚያደርጉ ምሰሶዎችን በትጋት እየተከሉ ይገኛሉ። የትግራይ ሰው እንዳያፈነግጥ የያዙበት ዘዴም፣ “አማራና ኦሮሞ ስልጣን ከያዘ ይፈጅሃል፣ ከቤትህ አፈናቀሎ ያባርርሃል!” የሚል የማያቋርጥ ሽብር በመንዛት ሲሆን፣ በዩኒቬርሲቲ፣ በውጭ ሃገራትና በክልል ከተሞች የተደራጁት የትግራይ ኮሚኒቲ ቋሚ አጀንዳዎችም፣ ህወሃት ከሌለ ኢትዮጵያዊነት አብሮ እንደሚያከትም የሚሰብኩ ናቸው።
“ወያኔ በሰራዊቱና በሲቪል ውስጥ ይህን ዘዴ በተደጋጋሚና በቀላሉ እንዴት ሊጠቀምበት ቻለ?” ለሚለው ጥያቄ መልሱ አሁንም ቀላል ነው። የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች የወያኔን ከፋፍሎ የመምታት ዘዴ ለማክሸፍ የሚያስችል ራእይ ያለው፣ የድርጊት ህብረት መፍጠር ባለመቻላቸው ነበር።
ከዚህ ከሰሞኑ ግርግር ጀርባ ያለው ታላቁ አጀንዳም ጽንፈኛ ሆነው የቆዩት ፖለቲከኞች ውስጥ ውስጡን በመግባባት ጎዳና ላይ መራመድ መጀመራቸውን በመረዳታቸው መሆኑ ግልፅ ነው። መለስን እስከዛሬ ስልጣን ላይ ይቆይ ዘንድ ያገዘችው የቁማር ካርድ አደጋ ላይ ወድቃለች። በመሆኑም መመኪያ አስማቱን ከሞት ለማትረፍ አዳዲስ የማደናቀፊያ እቅዶችን ነድፎ ብቅ አለ። የአባይ ግድብ አንዱ ነው።
መለስ ይሳካለት ይሆን?
ለዚህ ጥያቄ ከወዲሁ ምላሽ መስጠት አይቻልም። በዘር መከፋፈሉ በኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ የበለጠ እንዲቀጥል ጥረቱ ቀጥሎአል። በተለይ የሁለቱ አበይት ብሄሮች ህብረት አስጊ እየሆነ ስለመጣ፣ ያን ለመበተን በሙሉ ሃይላቸው ዘመቻ ጀምረዋል። በአሜሪካና በአውሮፓ የተቃውሞ ሰልፎች ላይ ኦሮሞዎች የኦነግን ባንዴራ መያዛቸውን እሳት ለመለኮሻ ሊጠቀሙበት ሲሞክሩ ተደምጠዋል። ትግሬዎችን በዘራቸውና በቋንቋቸው የሚያሽሟጥጡም ተሰምተዋል። መለስ የላካቸው የወያኔ ካድሬዎች፣ “አህያ! አህያ! ገና ትረገጣለህ! ገና ትገዛለህ!” እያሉ በአደባባይ ቁሻሻቸውን ሲያስታውኩ ታይተዋል። ፈቃደ ሸዋቀና የተባለ ግለሰብ በጨዋ ደንብ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ ስብሰባ ከተጠራ በሁዋላ፣ የአዳራሹ በር ላይ ሲደርስ “አንተማ የትግሬ ጠላት ነህ አትገባም” ተብሎ ሲከለከል፣ ጋዜጠኛው አዲሱ አበበ በጆሮው ሰምቶአል። “አህያ! ገና ትገዛለህ!” እያሉ የተሳደቡት የህወሃት ካድሬዎች ግን “ዘረኞች ናችሁና አትገቡም” ተብለው አልተከለከሉም። በዚህ ድርጊት ስሜታቸውን መያዝ ያልቻሉም፤ ተመሳሳይ ዘረኛ አባባሎችን ቢጠቀሙ ሊፈረድባቸው አይችልም። አንድ ዜጋ በሰው ሃገር ባይተዋር መሆኑ ሳይበቃው፣ በገዛ ሃገሩ ጉዳይ ላይ፣ “አይመለከትህም” ሲባል ከዚያ የከፋ መራራ ሁኔታ ሊገጥመው ከቶውንም አይችልም። ታማኝ በየነ እንባ እየተናነቀው፣ እንደ እሳት ሲንተከተክ ስሜቱን የማይገነዘብለት ሊኖር አይችልም። ይህን አይነት የዘር ግጭት አዝማሚያዎችን መለስ አጥብቆ ይፈልጋቸዋል።
ከእለታት አንድ ቀን አማራ እና ኦሮሞ የተባሉት ሁለቱ ግዙፍ ብሄሮች ህብረት ፈጥረው አንድ ሃይል ይሆኑ ይሆናል ብሎ መለስ መጠርጠሩ ወይም መስጋቱ አልቀረም። ይህ ስጋት እውን ከሆነ ትግራይን እንደ መጨረሻ መሸሻ ምሽግ ይዞ ለመቆየት ከወዲሁ ትግሬዎችን ከገዛ ወንድሞቻቸው ጋር ማናከሱን በተከታታይ ሲሰራበት ቆይቷል። ይህም አሁን የጀመረው አዲስ ስትራቴጂ አይደለም።
መለስ እስከ መጨረሻዋ ደቂቃ ማድረግ የሚችለውን ሁሉ መሞከሩ እንደማይቀር ከወዲሁ መረዳት ይገባል። መለስ የሃገሪቱን መሬት የሚቸበችብበት ሰይጣናዊ ምክንያቶች ይኖሩታል። ሙጋቤ የገበሬውን መሬት ለማስመለስ በመሞከሩ የሃገሪቱ ህዝብ የከፈለውን መራር ዋጋ የምናውቀው ነው። ተመሳሳይ ፈንጂ እየተቀበረልን ነው። ይሄ ግን እዳው ገብስ ነው። መለስ ኢትዮጵያ የተባለችውን ሃገር ህልውናዋን በጅምላ ከመሸጠም አይመለስም።
በተቃዋሚ የፖለቲካ መሪዎች በኩል እንደ ጀመሩት ልዩነታቸውን አቻችለው፣ ወደ መጨረሻው ግባቸው በትጋት ይጓዙ ይሆን?
በልበ ሙሉነት “ይቻላቸዋል!” ማለቱ ቢቸግርም ከበረቱና አሻግረው ማየት ከቻሉ ግን አያቅታቸውም። የውስጥ ትግሉ ፈታኝ ቢሆንም፣ ባላጋራቸው የዋዛ ባይሆንም፣ ሊፈፅሙት ይችላሉ። የኢትዮጵያ ህዝብ ለመስዋእትነት ዝግጁ እንደሆነ በተደጋጋሚ አስመስክሮአል። የመቻቻል ባህል ከመሪዎች ይጠበቃል። የእርስ በርስ ሽኩቻዎች ይቆሙ ዘንድ ይጠበቃል። ጉዞው ወደ ዴሞክራሲ ከሆነ፣ “የኔ ፖሊሲ ካንተ ፖሊስ ይሻላል!” የሚል ሙግት ጊዜውና ወቅቱ ሊሆን አይችልም። በዚህ ዘመን በፖሊሲ ልዩነት መናከስ ለመለስ ጠንካራ ጎን እገዛ ከማድረግ የዘለለ ውጤት አይኖረውም